Wednesday, August 5, 2015

ይድረስ ለጣይቱ



እኔ ነኝ ቦማርሌ
የጊታሬ ዜማ
ለዓለም የተሰማ
ፍቅር የሰበከ ሰላም የሰበከ
በመዋደድ ትግል ምርኮ የማረከ
እኔ ነኝ ቦማርሌ ለነፃነት ዜማ
ጊታሬ የሚሰማ፡፡
/////////////// 
አንቺ ነሽ ጣይቱ የነፃነት እናት
የክብር የሀገር የሰንደቅ እመቤት
የጦር ሜዳ መሪ
ጀግንነት ዘማሪ፡፡
////////////
ሰማሽ አንቺ ጣይቱ
ከሀበሻው ቀዬ ከእምብረቱ
እጄን ከፍ ያረኩቱ
እኔ ቦማርሌ ባንቺ ሀገር
እደመጣለው ስናገር፡፡
ከዛ ሆኖ እዚ ማዶ የጊታር ዜማን የሰማ
ያንቺው ህዝብ በኔ ተስማማ
የሰላም ዜማን አድምጦ ጊታሬ ልቡን ቢገዛው
በአክብሮት ሀውልት ያቆመ ሀበሻ እጅግ ለጋስ ነው
ሃበሻ እንዲህ ነው እንዴ
ነፃነቱን ለሰጠው ሳይሆን ስለ ነፃነት ላዜምኩ ለኔ
ለሀገሩ ለሞተ ሳይሆን ስለሀገሩ ላወራው ለኔ
ስንኙን የሚደረድር የሚያዜም መወድስ ቅኔ?
ጣይቱ ልሙትልሽ ሀበሻ አይከን አይወድም
የራሱን እየገደለ ለሌላ ነው የሚደክም
ለነፃነቱ የደማሽለት ህዝብሽ ካንቺ አብልጦኝ
ይሆን ሆይ እኔን ሊዘክር በሀገርሽ ሀውልት የሰጠኝ?
//////////////
ከነጊታሬ በክብሬ One Love እያልኩ ሳዜመው
ከሸገር ከከተምሽበት ሀውልቴን ከፍ ያደረገው
ላንቺ ግን ቦታ ጠቦታል ሀበሻ ስፍራም የለውም
የለገሽውን ሸገር ላንቺ ሀውልት አላደለውም::
ሰማሽኝ አንቺ ጣይቱ እኔም ዜማዬን እለጥቃለው
የነጻነት ብርሀን ይብራ ነጻነት ይታይ እላለው
የሰላም ሰንደቅ ይውለብለብ የነፃነት ሀውልትም ይቁም
አይከን ላለው ህዝብ ምልክት የነፃነቱም ትርጉም
አንቺ ነሽ ኩራት እናቱ
የጠላት ውጋት የህዝብ እረፍቱ
አንቺ ነሽ ውበት ድምቀቱ
የሰላም የነፃነቱ
አርማው አንቺ ጣይቱ፡፡


         ኤልያስ ታ.

          07/22/2015

Sunday, August 2, 2015

ተቀዶ የጠፋ ገፅ

---------------------
ከትልቅ ዶሴ ላይ ታሪክ ያጓደለ
ከመሀል ተነስቶ ለንባብ ያልዋለ
ከጥራዝ ከዶሴው ተለይቶ ያለ
ብዙ ታሪክ አለ።
-------------
ብዙ አለ ብዙ ገፅ ያልታየ ተቀዶ
ያልተነበበ ሀሳብ የቀረ ተማዶ
በባይተዋር አለም የገባ ያለቦታው
ብዙ አለ ብዙ ገፅ የጠፋ ከዶሴው
--------------
የተነጠለ ገጽ እውቀት እንደማይሆን
                        ታሪክ እንደማይሆን
ያልተሟላ ዶሴም ሙሉ እንደማይሆን
                        ጎዶሎ እንደሚሆን
ልብ ያላልን እኛ
የአንድ ዶሴን ታሪክ
በገፅ በምዕራፍ በቁጥር ተካፍለን
ቁንፅል ሀሳብ ሆነን
ጉንጥል ገጾች ሆነን

አለን! ብዙ አለን ተቀደን የጠፋን
ሆድ ብሶን ባይተዋር ጉንጥል ገፅ የሆንን
----------------
በባይተዋር ኑሮ በደመቀ ቀለም ተፅፎ መዘንጋት
የአንድ ዶሴ ታሪክ አጉድሎ ከመጥፋት
ከገፅ ዶሴነት
ከሀሳብ ታሪክነት
መሆኑ ባልከፋ
በጎዶሎ ገጾች ታሪክም ባልጠፋ።


                                 Elias T.
                                 New york 07/11/2015

Wednesday, July 22, 2015

ተንስዑ

ካለውበት ስፍራ የብረት ቅልጭታ እጅግ ከበዛበት
ግርግር ሁካታ ጎልቶ ከሞላበት
ይሰማኛል ዜማ የመቅደሱ ደውል
የካህኑን ፍታት ተከትሎ አሜን ሲል
ይሰማኛል ወገን በተመስጦ ሆኖ
ከደኙ ሲማጠን በፈጣሪው አምኖ
ይሰማኛል ከዚ ከጫጫታው መሀል
ተንስዑ የሚለው
ስገዱ የሚለው
                     የዲያቆኑ ቃጭል
ዲያቆኑ ለጥቋል
ወደ ምስራቅ እዩ ተመልከቱ ወደዛ
ይላል መሀል ቆሞ በእጣኑ መዓዛ
ከምዕራብ ያለው ከምስራቅ ርቄ
እኔ ከዚ ያለው ለዓለም ወድቄ
                      ዓለምን ናፍቄ
የምስራቁን ጥሪ የዲያቆኑን ዜማ
                       ለነፍስ የተስማማ
በናፈቀ ልቤ ባህር አሻግሬ
                 ተራራ አሳብሬ
የምስራቋን ሀገር ቅዳሴ አደምጣለው
የእጣን መዓዛን በማያውቅ አየር ውስጥ እጣን አሸታለው
ጉልበቴን በሀሳብ ከደጁ ሰድጄ ጌታ ሆይ እላለለው
እላለው እላለው እላለው እላለው።

              ኤልያስ .ታ
               07/22/2015

Thursday, July 9, 2015

የአርምሞ ቃላቶች

የአርምሞ ቃላቶች
----------------------
የባለ ቅኔው ጉልበቱ
የቃላት ውበት ፍሰቱ
ለሌላ ከሆነ እንጂ
አልበጀም አልሆነም ላንቺ
እንዲ ልኬት የማይሰጡት
ቃላት መርጠው ማይፈርጁት
ዜማ ደርሰው ማይዜሙት
ከመገለጥ በላይ ያለ
ከመወደስ ልቆ ያለ
ምን ይሉት ፍቅር ነው አንቺው አፍን በእጅ ያስከደነ
ቀልብን ሰርቆ የጠፋ ልብ ላይ ነግሶ የገነነ።
                /////////
ይህስ ቃል ከየት ነው የመጣ ፍቅርሽን ሊገልጥ የጣረ
ላይሆንለት ሚደክም አብዝቶ እንዲ የታተረ
አንድ ዘራፊ ይጥፋ ቅኔን በዜማ `ሚያሳምር
እማ ፍቅርሽን ገልጦ ብእሩን ላንቺ ሚሰድር
ነው ወይስ እናት ዜማ ነች ተደምጣ የማታበቃ?
እናት ቅኔ ነች ተፈታ የማታበቃ?
ነኝ
ለሷ መግለጫ ያጣው ፍቅሯን እንዲ ለማለት
አፌን በእጄ ከድኜ በአርምሞ የምቀኛት
እንዲህ ነው
አረምሟዊ ነው ዜማዬ ቅኔዬ ቃልም የለውም
ፍቅሯን በማይገልጥ ውዳሴ መውደዷን አላረክሰውም
ከመገለጥ በላይ ነው የሷ ከመተርጎም የላቀ
መውደዷን መቀበል እንጂ ለመግለጥስ የረቀቀ
እሷን መኖሩ ይበጃል በአርምሞ ውስጥ ተውጦ
እሷን ለማመስገኛ ቃላቱስ ከወዴት መጦ?
                 !!!!!!!
እንዲ ብቻ ልበልሽ እማ እኖርሻለው
አንቺን ለመግለጥ ቃል ብመርጥ ፍቅርሽን አሳንሳለው
በቃ እማ     ..........

በቃ።
                                 ኤ.ታ
                                May 2015
    

የከረረ ክራር

የከረረ ክራር
ታም…. ታራራራም…. ታራራም
ታራራራራም
ራምራምራም 
እራምራምራም
ይላል ያስናቁ ክራር
ጣቶቿ ጅማቱን ሲያከር
ስትገርፈው ቅኝት ቀይራ
ይላል ታራራራራራራራም ታራራም
አላወቀች እሷትዝታን ስትቃኝ
ክራሯን ስትገርፈው
አንጀቴን በጣቷ እንደነዘረችው
በትዝታ ይዛ ከዚ እዛ ማዶ እንዳሻገረችው
ታምራራራራም ራራም ራም እያለ ወደዛ
ከፍቅሬ መዓዛ
ከእቅፉ በታች ከመውደዷ ጋራ
ልቤን በልቧ አስራ
ትለኛለች ውዴ
            ውዴ የኔ ፍቅር
ከጎንክ እንደዋልኩ ከእቅፍህ ልደር?
ትለኛለች ነፍሴ
የሌት መወድሴ
የቀን መናፈቄ
በአስናቁ ክራር ተስላ ከፊቴ
ታምታራም ታራራም ታራራም ታረረረረም ራም ራምራምምም
የሚገረፍ ክራር የሚያለቅስ አንጀት
አንቺን ያሰበ ለት
ታራራም እያለ ትዝታሽን ይዞ
የተጕዝነው ጉዞ
በፍቅርሽ በናፍቆት የሰለለ ልቤ
እያለ ሚያዜም የሌት ቀን ርሀቤ
ዜማውን ያወርዳል ተቀበይ ትዝታ
የአስናቁን ክራር የአደመጥሽው ለታ
ርም ርም ርምርምርምርም
ማራኪ ፈገግታሽ ይኸው ፊቴ ግጥም
እኔ ደግሞ ግጥም ሥገጥም ሥገጥም
የሰማች አስናቁ ክራሯን አነሳች
ዜማዋን ለጠቀች
“አልሻም ማስንቆን የፈረስ ጭራ ነው
አልሻም ዋሽንትን ወንዝ ዳር በቃይ ነው
አምጡልኝ ክራሬን አንጀትን በአንጀት ነው”
አለች ክራሯን ገረፈች
አንጀቴን ገረፈች
አንቺን የናፈቀ ነፍሴን እህ አስባለች
ክራሩ ከረረ ናፍቆቴ ከረረ
ይህንን የሰማ ክራር ተናገረ
አንቺን የናፈቀ
በናፍቆት አለቀ፡፡
                        ኤልያስ ታ.
                        06/25/2015

Sunday, April 26, 2015

አቤቱ የሆነብኝን አስብ

አቤቱ የሆነብኝን አስብ

በጲላጦስ ፍርድ ላይ በሀሰት ስትወነጀል
ጀርባክ በጅራፍ ደምቶ ጉልበትክ በዳገት ሲዝል
አብራክ እንደደማችው በሀዘን ውስጧ ተሰብሮ
እንደ አዛኝቷ እናትክ ሀዘኗ ለሆነክ አብሮ
እነደሷ እኔም አነባው ልቤ በሀዘን ደማ
የምናገረው ላይኖረኝ ልጄ በሞት ተቀማ
… አቤቱ የሆነብኝን አስብ…
የሚፈስ ጣሪያዬን ሊደፍን ከእቅፌ እርቆ የሄደ
ምስኪኑ ያብራኬ ክፋይ በረሀ ገብቶ ወደቀ
ማተቡን እንዳጠበቀ…
… እጆችክ ከመስቀል ጋራ በምስማር ሲቸነከሩ
አካል በደም ተሞልቶ አጥንቶች ሲቆጠሩ
በእንባ የተሞላችው አንጀቷ ችሎ ያልቻለው
እናትክ ስንቱን አየችው
እኔም ምስኪኑ ልጄ እቅፌን ገና ያልጠገበው
አንገቱ በካራ ስለት ሲታረድ እንዴት ልቻለው
መሶቤን ሙሉ ሊያደርግ በረሀ ገብቶ የቀረ
ለኔ ሊያሳልፍ ሲጥር ባንገቱ ካራ አለፈ
እንዴት ልቻለው ከቶ የልጄን መታረድ ባይኔ
የደሙን መፈሰስ እያየው ጠፈብኝ የለቅሶ ወኔ
ልጄ ክብሬ ማረጌ የአይኔ ማረፊያ ሀብቴ
ስቅታው የሚያባንነኝ ተቀላ ይህው ከፊቴ
… አቤቱ የሆነብኝን አስብ …
ልጄ ስልጣን የለውም ሞትን ድል አርጎ አይመጣም
ዳግም ከእቅፌ ሆኖ እናቴ እነሆኝ አይልም
ታድያ ለዚ ምስኪን ደም ባህሩን ቀይ ላረገ
ሀሳቡን ከጫፍ ሳያደርስ በእንጭጩ ለጠወለገ
ምላሽክ አይዘግይ ጌታ ሆይ.. የፍርድህን ቀን አቅርብ
አቤቱ እለምናለው የሆነብኝን አስብ፡፡


 በሊቢያ በረሀ አርገው ወደ ፈጣሪያቸው ላቀኑ ሰማህታት።

                                                                              ኤ..ታ   04/22/2015

Monday, March 23, 2015

መንገድተኛ ልጅሽ

መንገድተኛ ልጅሽ

ቀኝ አውለኝ ብሎ በናት ባባት ጠሎት ከቤቱ የወጣ
ምስኪኑ ወዳጄ መንገድ ግራ አጋብቶት ቀረ እንደወጣ
ይህ ምስኪን ወንድሜ በሀገሩ በቀዬው ስንቱን መንገድ መርቶ
መንገድ ለጠፋቸው መንገዱን አብርቶ
ስንቱን እንዳልሸኘ
ዛሬ በሰው ሀገር  በመንገድ ተሞኘ
 ይህ መንገድ አዋቂ
እግር አስታራቂ
ቢጠፉ ወዴት ባይ
ቢስቱ አለው ባይ
ዛሬ በሰው ሀገር ሰኔው ከሰኞ ጋር አብረው ቢያብሩበት
ወጦ አልተመለሰም መሄጃው ጠፋበት!!
… ሰማሽ አንቺ ምስኪን እናት አንቺ ምስኪን ሀገር
ልጅሽ መንገድ ገብቶ እንደወጣ ሲቀር
ያ ከጋራ ሸንተረር ቀበሌ አቋርጦ
ወረዳን አሳብሮ
ካሻው መንደር ዘልቆ
ካሻው ቀዬ አድሮ
ወዳሻው የሚበር
ያ ደፋሩ ልጅሽ ጠፋብሽ አንቺ ሀገር!!
…ሲናገር ኩራቱ ግርማ ሞገስ ያለው
ምስኪኑ ወንድሜ ዛሬ በሰው ሀገር እሱ ሌላ ሰው ነው!!
..ፈገግታው ምድር የሚያሞቅ
ጨዋታው ሀዘን ሚያርቅ
ያ ሞገሱ ሞልቶ የሚታይ ለቀዬው ድምቀት የሆነ
ልጅሽ አንገቱን ደፍቷል ያስባል እንደመከነ

ህመሙን እንዴት ፤ልንገርሽ
መጥፋቱን እንዴት ላስረዳሽ
አታውቂማ አንቺ ተሰደሽ
ህዝብሽን ባለበት ትተሸ
ወደሌላው እየተጓዝሽ ከመንገድ ጠፍተሽ አታውቂም
የስደት ውሉ፤ ስሜቱ ሀገሬ አንቺ አይገባሽም
…. ከህዝብሽ እርቀሽ ሄደሽ ‘’አወይ የህዝቤ ሆታ
የባህል ጭፈራው ዝላዩና እስክስታ’’
ብለሽ ናፍቀሽ ታውቂያለሽ ?
አታውቂም!!  ስደት ላንቺ አይገባሽም
ተሰደሽ ስለማታውቂ ህመሙ አይሰማሽም!!
…ይህው ምስኪኑ ልጅሽ መንገድ መሪው
                                 ለቀዬው
መንገድ አስቶት ቆሟል
መሄጃው ግራ ገብቶታል
እናም አንቺ ሀገሬ ውጪና
ከህዝብሽ ተሰደጂና
የስደት ጠአሙን ቀምሰሽ
ልጆችሽን ሰብስቢና
መንገድ መሪው ልጅሽን
መንገድሽን አሳይውና
ሙቀትሽ የራቀው ሁሉ ከጉያሽ መሀል ገብቶ
አንገቱን ያቀረቀረም በኩራት ድምጡ አቅራርቶ
ሀገሬ ይበል በሀይሎጋ
የሁሉም ማማር አንቺው ጋ. ፡፡
                                                                                                                            ኤልያስ  ታ.                                                                                      03/08/2015  10:20 PM

አንድ ወንድሜ ከመንገድ ላይ መሄጃው ጠፍቶት ባጋጠመኝ ግዜ የተሰማኝ ስሜት ነው! ስንቱ በሰው ሀገር እንደጠፋ ቀርቷል!




!