Thursday, February 9, 2017

የተወጠረ እንባ


በሰዓሊ ሸራ ተወጥሮ ሚታይ የቆንጆ ልጅ እንባ
ሸራውን ያራሰ
ቀለም የጨረሰ ሀዘኗ ሚጋባ
ይታየኛል ለቅሶ
 ከግድግዳው መሀል በቀለም ርሶ።
የዚችን ውብ ልጅ ገፅ እንዲህ ያጨለመ
ያማሩ ዓይኖቿን በእንባ ያደከመ
ምን ያለ ሰዓሊ ምን ያለ ቀቢ ነው
እንዴት ብትፈትነው እንዴት ቢጣላት ነው?
መሳም የሚጎዳው የመሰለ ጉንጯ በእንባ ይታጠባል
ሰዓሊው ወይ በሀዘን ወይ በደስታ ሆኖ ቀለም ይጨርሳል
ይህን የሚታዘብ ምስኪን እድምተኛ
በሰዓሊ ብሩሽ ለሆነ መናኛ
ለሚፈስ እልፍ እንባ ቆሞ ይተክዛል
ይህ ማራኪ ውበት ከማንባቱ በፊት እንደምን ይመስላል
እንደው ስቆ ያውቃል
ብሎ ይጠይቃል?

ሰዓሊ አሁን ሳቀ
የማያቀውን ፊት ለማወቅ ናፈቀ
ስቆ ማያቅን ፊት በሳቅ አጠየቀ
ሊያስቃት የሚችል
ሊያስነባት የሚችል
ህይወቷን በብሩሽ ቆርጦ የሚቀጥል
ሰዓሊ ናፈቀ
ስቆ ማያቅ ፊቷን በሳቅ ውስጥ ፈለገ
ትስቅ ይሆን እሷ
እንባዋስ ይቆማል
ሰዓሊ እጅግ ጓጉቷል
ምስኪን እድምተኛ ወደላይ አንጋጧል
መሳል ተጀመረ........


ኤታ
02/09/2017

Sunday, May 15, 2016

ተቀበል


የማስንቆ ዜማ
ደምቆ ከተሰማ
ይልኻል ተቀበል
የቅኔውን ማዕበል
“ሀገሬ ዜማነሽ ሀገሬ ውብ ቅኔ
ያዜሙሽ ይዘርፉሽ የበዛልሽ ፍሬ”
ይላል ባለስንኝ ሞጋች ሀሳብ ያለው
ተቀባይ ካገኘ ድምጡን ከፍ ያረገው
የማስንቆ ጅማት በዜማ ሲዋዛ
የባለቅኔ ቃል ከሀሳብ ሲነሳ
ይልኻል ተቀበል ተቀበል ጨዋታ
እየሳቀ ሚያለቅስ የኑሮ እውነታ::
እዚም ጨዋታ አለ
በማስንቆ ያይደለ
በጭብጫቦ ያይደለ
ዜማ ያልታደለ
እዚም ጨዋታ አለ
ተቀበል ይልኻል
ከዘማኞች መንደር
በነ ፈስብክ ሀገር
እውቀትና ስድብ የተሰናሰኑ
በቧልትና እውነት እጣን የታጠኑ
ለፌዝና ስድብ ተማርኮ የተረታ
እዚ አለ ጨዋታ                                                                                        https://youtu.be/jzRA5IEj_qY
ይኸው እዚኛው ጥግ
ከመፅሀፍ ርዕስ የተገኘ እውቀት
በአሉባልታ ወሬ የታፈነ ግምት
ተቀበል ይልኻል የማወቁን ልኬት
ደግሞ በዚኛው ጫፍ ከሀይማኖት ግድግዳ
ከኔ እበልጥ እኔ እኔ በልጥ የአማኞች ሽኩቻ
ቅዱስ ቃል ከስድብ ከቧልት ተዳምሮ
ላጥምቅህ ይልኻል ከሀይማኖት ጏሮ
ተቀበል እዚ ጋር
የፖለቲካን ጥግ የሀገርን ችግር ተንታኝ ዲስኩረኛ
የመንግስትን ችግር ፈትፋች ታምረኛ
ተቀበል ይልኻል መፍትሄ ለሀገር
ለምስኪኑ ወገን፡፡
መሰንቆ ባትሰማ
ባይኖረውም ዜማ
ተቀበል ይህንን ጀግንነት
ሁሉን አዋቂነት
ሁሉን ሰዳቢነት
ሁሉን ተንታኝነት
ተቀበል
ሀገር ሲቃጠል ሰልፊ
ደገፍ ብለ- ብትነሳ
የሚወድልክ እልፍ ነው
ለላይክ እጁ ማይሳሳ
መታደል እኮ ነው እናንተው
ስንት ደራሲ --- ስንት ሀያሲ
ስንት ገጣሚ --- ስንት አራሚ
ስንት ለጣፊ--- ስንት ጠሀፊ
ስንት ጀግና የጦር መሪ
ድንበር አፍራሽ ድንበር ሰሪ
ባለ ብዙ ግብረ ብዙ
ሀሳብ ብዙ ስድበ ብዙ
ጠብ ደሞዙ
የዘመነ ባለ ዜማው
ቅኝተ ብዙ ፌስቡከኛው
ይልኻል ተቀበለኝ
ሀገርን በላይክ ብዛት በኮመንት ሊተምንልኝ
              ተቀበል፡፡
    
                       ኤልያስ ታ.
                      04/28/2016



ብርሃን ናፋቂዎች

          
የጨለመ ጨልሞ አይቀር ይነጋል ብለው ቢያወሩ
ሌቱን ለማንጋት ብለው ስንቶች ሲገፉ አደሩ
የንጋት ወጋገን ናፍቋቸው እድሜ ህይወታቸውን ገበሩ፡፡
“ብርሀን ከሩቅ አይተናል” ያሉም ሰባ ሰገሎች
መንጋውን ተከተል ብለው ከግመል ወጡ ጥቂቶች
ጨልሞ አይቀር የተባለን ሌቱንም ለመግፊያ ብለው
ጥቂቶች ከግመል ያሉ መንጋውን በተራ ማግደው
ከግመላቸው ጋራ ይሞቃሉ እሳት ከበው::
ይህ ጨለማን ገፊ መንጋ ነገን ሊያይ ተስፋ የጣለ
በዛሬ ድቅድቅ መሆን ውስጥ በነገ ተስፋ ያመነ
በዘመን መፈራረቅ ውስጥ ጨለማን ሲገፋ ኖረ::
የሰባ ሰገሉን ምሪት የጥበበኞቹን መንገድ
አናምንም ብለው የካዱ
ብርሀናቸውን ፍለጋ በአሸዋው ባህር ነጎዱ
እኒ የብርሀና ሕይወት ተስፈኞች
ግብዓታቸውን በባህር ወስብሀት ብለው ያሉ
ነገ ብርሀን ሊሆን በነፍስያቸው ያምናሉ
ለሰባ ሰገሉ የታመኑ እናንተው ትመሩን ብለው
ሌቱን ሊገፉ የጣሩ
በውድቅት ተኩላ በልቷቸው በደም ርሰው አደሩ
ባለ ግመሉን የናቁ
ተኩሎች መንጋ ነጠቁ
ጨቅሎችን ከእናት አራቁ
በመንጋው መበታተን ውስጥ ክፉዎች ደማቅ ሳቅ ሳቁ 
መንጋው ይነጋል ብሎ ሰባ ሰገሉን አምኖ
ጨለማን እገፋ ብሎ የነገን ብርሀን ናፍቆ
ሲገፋ ሲገፋ ያድራል አንጀቱን ከሆዱ አጣብቆ
ቀና ሲል ሰማይ ይሸሻል
ቢያንጋጥጥ ከርሱ እንባ በቀር
ጠብ የሚል ከሰማይ ጠፍቷል
ተኩላ ልጁን ይነጥቃል
ባህር ልጁን ይወስዳል
ይህም ሁሉ እየሆን ሰባሰገሉን ያሞቃል
መንጋው
ጨለማን እገፋ ብሎ
ብርሀን አገኘው ብሎ
ተስፋውን በተስፋ ጥሎ
ይገፋል
ይገፋል
ወይ ያልፋል
ወይ ያልፋል፡፡
  
                                      ኤልያስ ታ.
                                      04 18 16
         ስጋችንን የለመደው ሜዲትራንያን ዛሬም ብዙዎቼን በወሰደ ግዜና ጋምቤላ ያሉ ሁሉ በፅልመት በተሸፈኑ ግዜ ተፃፈ፡፡


Sunday, February 14, 2016

አንድ ማኪያቶ


------------------
ውዴ እዛች ካፌ

ፈገግታ የማታውቅ የቤቱ አሳላፊ

ምን ልታዘዝ ያለች ትሪ ይዛ ሰፊ

አንድ ማኪያቶ ከአንድ ጣፋጭ ኬክ ጋር

ቡና እንደወረደ ያልገባበት ስኳር

ይዛ የተመለሰች

አውግተን አውግተን  ከጨረስን ነበር፡፡

ትኩስ ማኪያቶ ቡና ያልበዛበት ወተቱ ያላነሰ

ውበቱ የሚማርክ ለአይን ያልደፈረሰ

ከግራ ወደቀኝ ታማስይው ነበር

ከጨመርሽው ስኳር፡፡

ፈገግታ የማታውቅ ያቺ አሳላፊ

ማንኪያ ታመጣለች ማንኪያ እየወሰደች

ላንቺ ፈገግ ብላ እኔን ገላመጠች

.….ይህ ...ትኩስ ማኪያቶ

ወተቱ ከቡናው ቡናው ከወተቱ የተሰናሰለ

ከውስጡ አንደኛውን ማውጣት ማነው የቻለ?

ቡናውን ከወተት ማነው የነጠለ?

አየሽ ከግራ ወደቀኝ ከላይም ወደታች

በማንኪያ ቢማሰል

ይዋሀዳል እንጂ ከቶም አይነጠል፡፡



አየሽው ባሬስታው የማሽኑ ጌታ

ይህ ባለችሎታ

ማኪያቶ ቢሉሽ ማኪያቶ ነው  ከልቡ ሚሰራ

ወተቱን ከቡና ቡናውን ከወተት ያኖረ በጋራ

ይህም የኛ ዓለም ነው

የማሽኑ ጌታ እርሱ ከሰማይ ነው

እኔ ያንቺ ቡና አንቺ የኔ ወተት

እርሱ የሰራውን ይህን ማኪያቶ አይለየውም ዘበት

አየሽው ባሬስታው አየሽው ጥበቡን

ምን ማንኪያ ቢበዛ አማሳይ መሀሉን

ሊለየው እንዳይችል ቡናና ወተቱን

ድንቅ አድርጎ ነው መጥኖ ያዋሀደ

ባሬስታው እርሱ ነው ሁሉን የፈቀደ፡፡



                ኤልያስ.ታ
                             02/14/2016
                                       EK

Wednesday, August 5, 2015

ይድረስ ለጣይቱ



እኔ ነኝ ቦማርሌ
የጊታሬ ዜማ
ለዓለም የተሰማ
ፍቅር የሰበከ ሰላም የሰበከ
በመዋደድ ትግል ምርኮ የማረከ
እኔ ነኝ ቦማርሌ ለነፃነት ዜማ
ጊታሬ የሚሰማ፡፡
/////////////// 
አንቺ ነሽ ጣይቱ የነፃነት እናት
የክብር የሀገር የሰንደቅ እመቤት
የጦር ሜዳ መሪ
ጀግንነት ዘማሪ፡፡
////////////
ሰማሽ አንቺ ጣይቱ
ከሀበሻው ቀዬ ከእምብረቱ
እጄን ከፍ ያረኩቱ
እኔ ቦማርሌ ባንቺ ሀገር
እደመጣለው ስናገር፡፡
ከዛ ሆኖ እዚ ማዶ የጊታር ዜማን የሰማ
ያንቺው ህዝብ በኔ ተስማማ
የሰላም ዜማን አድምጦ ጊታሬ ልቡን ቢገዛው
በአክብሮት ሀውልት ያቆመ ሀበሻ እጅግ ለጋስ ነው
ሃበሻ እንዲህ ነው እንዴ
ነፃነቱን ለሰጠው ሳይሆን ስለ ነፃነት ላዜምኩ ለኔ
ለሀገሩ ለሞተ ሳይሆን ስለሀገሩ ላወራው ለኔ
ስንኙን የሚደረድር የሚያዜም መወድስ ቅኔ?
ጣይቱ ልሙትልሽ ሀበሻ አይከን አይወድም
የራሱን እየገደለ ለሌላ ነው የሚደክም
ለነፃነቱ የደማሽለት ህዝብሽ ካንቺ አብልጦኝ
ይሆን ሆይ እኔን ሊዘክር በሀገርሽ ሀውልት የሰጠኝ?
//////////////
ከነጊታሬ በክብሬ One Love እያልኩ ሳዜመው
ከሸገር ከከተምሽበት ሀውልቴን ከፍ ያደረገው
ላንቺ ግን ቦታ ጠቦታል ሀበሻ ስፍራም የለውም
የለገሽውን ሸገር ላንቺ ሀውልት አላደለውም::
ሰማሽኝ አንቺ ጣይቱ እኔም ዜማዬን እለጥቃለው
የነጻነት ብርሀን ይብራ ነጻነት ይታይ እላለው
የሰላም ሰንደቅ ይውለብለብ የነፃነት ሀውልትም ይቁም
አይከን ላለው ህዝብ ምልክት የነፃነቱም ትርጉም
አንቺ ነሽ ኩራት እናቱ
የጠላት ውጋት የህዝብ እረፍቱ
አንቺ ነሽ ውበት ድምቀቱ
የሰላም የነፃነቱ
አርማው አንቺ ጣይቱ፡፡


         ኤልያስ ታ.

          07/22/2015

Sunday, August 2, 2015

ተቀዶ የጠፋ ገፅ

---------------------
ከትልቅ ዶሴ ላይ ታሪክ ያጓደለ
ከመሀል ተነስቶ ለንባብ ያልዋለ
ከጥራዝ ከዶሴው ተለይቶ ያለ
ብዙ ታሪክ አለ።
-------------
ብዙ አለ ብዙ ገፅ ያልታየ ተቀዶ
ያልተነበበ ሀሳብ የቀረ ተማዶ
በባይተዋር አለም የገባ ያለቦታው
ብዙ አለ ብዙ ገፅ የጠፋ ከዶሴው
--------------
የተነጠለ ገጽ እውቀት እንደማይሆን
                        ታሪክ እንደማይሆን
ያልተሟላ ዶሴም ሙሉ እንደማይሆን
                        ጎዶሎ እንደሚሆን
ልብ ያላልን እኛ
የአንድ ዶሴን ታሪክ
በገፅ በምዕራፍ በቁጥር ተካፍለን
ቁንፅል ሀሳብ ሆነን
ጉንጥል ገጾች ሆነን

አለን! ብዙ አለን ተቀደን የጠፋን
ሆድ ብሶን ባይተዋር ጉንጥል ገፅ የሆንን
----------------
በባይተዋር ኑሮ በደመቀ ቀለም ተፅፎ መዘንጋት
የአንድ ዶሴ ታሪክ አጉድሎ ከመጥፋት
ከገፅ ዶሴነት
ከሀሳብ ታሪክነት
መሆኑ ባልከፋ
በጎዶሎ ገጾች ታሪክም ባልጠፋ።


                                 Elias T.
                                 New york 07/11/2015