መንገድተኛ ልጅሽ
ቀኝ አውለኝ ብሎ በናት ባባት ጠሎት ከቤቱ የወጣ
ምስኪኑ ወዳጄ መንገድ ግራ አጋብቶት ቀረ እንደወጣ
ይህ ምስኪን ወንድሜ በሀገሩ በቀዬው ስንቱን መንገድ
መርቶ
መንገድ ለጠፋቸው መንገዱን አብርቶ
ስንቱን እንዳልሸኘ
ዛሬ በሰው ሀገር በመንገድ ተሞኘ
ይህ መንገድ አዋቂ
እግር አስታራቂ
ቢጠፉ ወዴት ባይ
ቢስቱ አለው ባይ
ዛሬ በሰው ሀገር ሰኔው ከሰኞ ጋር አብረው ቢያብሩበት
ወጦ አልተመለሰም መሄጃው ጠፋበት!!
… ሰማሽ አንቺ ምስኪን እናት አንቺ ምስኪን ሀገር
ልጅሽ መንገድ ገብቶ እንደወጣ ሲቀር
ያ ከጋራ ሸንተረር ቀበሌ አቋርጦ
ወረዳን አሳብሮ
ካሻው መንደር ዘልቆ
ካሻው ቀዬ አድሮ
ወዳሻው የሚበር
ያ ደፋሩ ልጅሽ ጠፋብሽ አንቺ ሀገር!!
…ሲናገር ኩራቱ ግርማ ሞገስ ያለው
ምስኪኑ ወንድሜ ዛሬ በሰው ሀገር እሱ ሌላ ሰው
ነው!!
..ፈገግታው ምድር የሚያሞቅ
ጨዋታው ሀዘን ሚያርቅ
ያ ሞገሱ ሞልቶ የሚታይ ለቀዬው ድምቀት የሆነ
ልጅሽ አንገቱን ደፍቷል ያስባል እንደመከነ
ህመሙን እንዴት ፤ልንገርሽ
መጥፋቱን እንዴት ላስረዳሽ
አታውቂማ አንቺ ተሰደሽ
ህዝብሽን ባለበት ትተሸ
ወደሌላው እየተጓዝሽ ከመንገድ ጠፍተሽ አታውቂም
የስደት ውሉ፤ ስሜቱ ሀገሬ አንቺ አይገባሽም
…. ከህዝብሽ እርቀሽ ሄደሽ ‘’አወይ የህዝቤ ሆታ
የባህል ጭፈራው ዝላዩና እስክስታ’’
ብለሽ ናፍቀሽ ታውቂያለሽ ?
አታውቂም!! ስደት
ላንቺ አይገባሽም
ተሰደሽ ስለማታውቂ ህመሙ አይሰማሽም!!
…ይህው ምስኪኑ ልጅሽ መንገድ መሪው
ለቀዬው
መንገድ አስቶት ቆሟል
መሄጃው ግራ ገብቶታል
እናም አንቺ ሀገሬ ውጪና
ከህዝብሽ ተሰደጂና
የስደት ጠአሙን ቀምሰሽ
ልጆችሽን ሰብስቢና
መንገድ መሪው ልጅሽን
መንገድሽን አሳይውና
ሙቀትሽ የራቀው ሁሉ ከጉያሽ መሀል ገብቶ
አንገቱን ያቀረቀረም በኩራት ድምጡ አቅራርቶ
ሀገሬ ይበል በሀይሎጋ
የሁሉም ማማር አንቺው ጋ. ፡፡
ኤልያስ ታ. 03/08/2015 10:20 PM
አንድ ወንድሜ ከመንገድ ላይ መሄጃው ጠፍቶት ባጋጠመኝ ግዜ የተሰማኝ ስሜት ነው! ስንቱ በሰው ሀገር እንደጠፋ ቀርቷል!
!
