Sunday, May 15, 2016

ተቀበል


የማስንቆ ዜማ
ደምቆ ከተሰማ
ይልኻል ተቀበል
የቅኔውን ማዕበል
“ሀገሬ ዜማነሽ ሀገሬ ውብ ቅኔ
ያዜሙሽ ይዘርፉሽ የበዛልሽ ፍሬ”
ይላል ባለስንኝ ሞጋች ሀሳብ ያለው
ተቀባይ ካገኘ ድምጡን ከፍ ያረገው
የማስንቆ ጅማት በዜማ ሲዋዛ
የባለቅኔ ቃል ከሀሳብ ሲነሳ
ይልኻል ተቀበል ተቀበል ጨዋታ
እየሳቀ ሚያለቅስ የኑሮ እውነታ::
እዚም ጨዋታ አለ
በማስንቆ ያይደለ
በጭብጫቦ ያይደለ
ዜማ ያልታደለ
እዚም ጨዋታ አለ
ተቀበል ይልኻል
ከዘማኞች መንደር
በነ ፈስብክ ሀገር
እውቀትና ስድብ የተሰናሰኑ
በቧልትና እውነት እጣን የታጠኑ
ለፌዝና ስድብ ተማርኮ የተረታ
እዚ አለ ጨዋታ                                                                                        https://youtu.be/jzRA5IEj_qY
ይኸው እዚኛው ጥግ
ከመፅሀፍ ርዕስ የተገኘ እውቀት
በአሉባልታ ወሬ የታፈነ ግምት
ተቀበል ይልኻል የማወቁን ልኬት
ደግሞ በዚኛው ጫፍ ከሀይማኖት ግድግዳ
ከኔ እበልጥ እኔ እኔ በልጥ የአማኞች ሽኩቻ
ቅዱስ ቃል ከስድብ ከቧልት ተዳምሮ
ላጥምቅህ ይልኻል ከሀይማኖት ጏሮ
ተቀበል እዚ ጋር
የፖለቲካን ጥግ የሀገርን ችግር ተንታኝ ዲስኩረኛ
የመንግስትን ችግር ፈትፋች ታምረኛ
ተቀበል ይልኻል መፍትሄ ለሀገር
ለምስኪኑ ወገን፡፡
መሰንቆ ባትሰማ
ባይኖረውም ዜማ
ተቀበል ይህንን ጀግንነት
ሁሉን አዋቂነት
ሁሉን ሰዳቢነት
ሁሉን ተንታኝነት
ተቀበል
ሀገር ሲቃጠል ሰልፊ
ደገፍ ብለ- ብትነሳ
የሚወድልክ እልፍ ነው
ለላይክ እጁ ማይሳሳ
መታደል እኮ ነው እናንተው
ስንት ደራሲ --- ስንት ሀያሲ
ስንት ገጣሚ --- ስንት አራሚ
ስንት ለጣፊ--- ስንት ጠሀፊ
ስንት ጀግና የጦር መሪ
ድንበር አፍራሽ ድንበር ሰሪ
ባለ ብዙ ግብረ ብዙ
ሀሳብ ብዙ ስድበ ብዙ
ጠብ ደሞዙ
የዘመነ ባለ ዜማው
ቅኝተ ብዙ ፌስቡከኛው
ይልኻል ተቀበለኝ
ሀገርን በላይክ ብዛት በኮመንት ሊተምንልኝ
              ተቀበል፡፡
    
                       ኤልያስ ታ.
                      04/28/2016



ብርሃን ናፋቂዎች

          
የጨለመ ጨልሞ አይቀር ይነጋል ብለው ቢያወሩ
ሌቱን ለማንጋት ብለው ስንቶች ሲገፉ አደሩ
የንጋት ወጋገን ናፍቋቸው እድሜ ህይወታቸውን ገበሩ፡፡
“ብርሀን ከሩቅ አይተናል” ያሉም ሰባ ሰገሎች
መንጋውን ተከተል ብለው ከግመል ወጡ ጥቂቶች
ጨልሞ አይቀር የተባለን ሌቱንም ለመግፊያ ብለው
ጥቂቶች ከግመል ያሉ መንጋውን በተራ ማግደው
ከግመላቸው ጋራ ይሞቃሉ እሳት ከበው::
ይህ ጨለማን ገፊ መንጋ ነገን ሊያይ ተስፋ የጣለ
በዛሬ ድቅድቅ መሆን ውስጥ በነገ ተስፋ ያመነ
በዘመን መፈራረቅ ውስጥ ጨለማን ሲገፋ ኖረ::
የሰባ ሰገሉን ምሪት የጥበበኞቹን መንገድ
አናምንም ብለው የካዱ
ብርሀናቸውን ፍለጋ በአሸዋው ባህር ነጎዱ
እኒ የብርሀና ሕይወት ተስፈኞች
ግብዓታቸውን በባህር ወስብሀት ብለው ያሉ
ነገ ብርሀን ሊሆን በነፍስያቸው ያምናሉ
ለሰባ ሰገሉ የታመኑ እናንተው ትመሩን ብለው
ሌቱን ሊገፉ የጣሩ
በውድቅት ተኩላ በልቷቸው በደም ርሰው አደሩ
ባለ ግመሉን የናቁ
ተኩሎች መንጋ ነጠቁ
ጨቅሎችን ከእናት አራቁ
በመንጋው መበታተን ውስጥ ክፉዎች ደማቅ ሳቅ ሳቁ 
መንጋው ይነጋል ብሎ ሰባ ሰገሉን አምኖ
ጨለማን እገፋ ብሎ የነገን ብርሀን ናፍቆ
ሲገፋ ሲገፋ ያድራል አንጀቱን ከሆዱ አጣብቆ
ቀና ሲል ሰማይ ይሸሻል
ቢያንጋጥጥ ከርሱ እንባ በቀር
ጠብ የሚል ከሰማይ ጠፍቷል
ተኩላ ልጁን ይነጥቃል
ባህር ልጁን ይወስዳል
ይህም ሁሉ እየሆን ሰባሰገሉን ያሞቃል
መንጋው
ጨለማን እገፋ ብሎ
ብርሀን አገኘው ብሎ
ተስፋውን በተስፋ ጥሎ
ይገፋል
ይገፋል
ወይ ያልፋል
ወይ ያልፋል፡፡
  
                                      ኤልያስ ታ.
                                      04 18 16
         ስጋችንን የለመደው ሜዲትራንያን ዛሬም ብዙዎቼን በወሰደ ግዜና ጋምቤላ ያሉ ሁሉ በፅልመት በተሸፈኑ ግዜ ተፃፈ፡፡


Sunday, February 14, 2016

አንድ ማኪያቶ


------------------
ውዴ እዛች ካፌ

ፈገግታ የማታውቅ የቤቱ አሳላፊ

ምን ልታዘዝ ያለች ትሪ ይዛ ሰፊ

አንድ ማኪያቶ ከአንድ ጣፋጭ ኬክ ጋር

ቡና እንደወረደ ያልገባበት ስኳር

ይዛ የተመለሰች

አውግተን አውግተን  ከጨረስን ነበር፡፡

ትኩስ ማኪያቶ ቡና ያልበዛበት ወተቱ ያላነሰ

ውበቱ የሚማርክ ለአይን ያልደፈረሰ

ከግራ ወደቀኝ ታማስይው ነበር

ከጨመርሽው ስኳር፡፡

ፈገግታ የማታውቅ ያቺ አሳላፊ

ማንኪያ ታመጣለች ማንኪያ እየወሰደች

ላንቺ ፈገግ ብላ እኔን ገላመጠች

.….ይህ ...ትኩስ ማኪያቶ

ወተቱ ከቡናው ቡናው ከወተቱ የተሰናሰለ

ከውስጡ አንደኛውን ማውጣት ማነው የቻለ?

ቡናውን ከወተት ማነው የነጠለ?

አየሽ ከግራ ወደቀኝ ከላይም ወደታች

በማንኪያ ቢማሰል

ይዋሀዳል እንጂ ከቶም አይነጠል፡፡



አየሽው ባሬስታው የማሽኑ ጌታ

ይህ ባለችሎታ

ማኪያቶ ቢሉሽ ማኪያቶ ነው  ከልቡ ሚሰራ

ወተቱን ከቡና ቡናውን ከወተት ያኖረ በጋራ

ይህም የኛ ዓለም ነው

የማሽኑ ጌታ እርሱ ከሰማይ ነው

እኔ ያንቺ ቡና አንቺ የኔ ወተት

እርሱ የሰራውን ይህን ማኪያቶ አይለየውም ዘበት

አየሽው ባሬስታው አየሽው ጥበቡን

ምን ማንኪያ ቢበዛ አማሳይ መሀሉን

ሊለየው እንዳይችል ቡናና ወተቱን

ድንቅ አድርጎ ነው መጥኖ ያዋሀደ

ባሬስታው እርሱ ነው ሁሉን የፈቀደ፡፡



                ኤልያስ.ታ
                             02/14/2016
                                       EK